FOR BETTER OROMIA

ዘርአይ ደረስ – ግማሽ ተረት

ተስፋዬ ገብረአብ (Gadaa)*

በ2014 አጋማሽ በዋሽንግተን ዲሲ ቆይታዬ “ታሪክ እና ተረት – በአፍሪቃ ቀንድ” በሚል ርእስ በECC (Eritrean Comunity Center) አዳራሽ ከኤርትራውያን ጋር አጭር ቆይታ አድርጌ ነበር። በሴሚናሩ ላይ ከተዋወቅሁዋቸው ኤርትራውያን መካከል ሶፊያ ተስፋማርያም አንዷ ነበረች። በሶስተኛው ቀን በድጋሚ ተገናኝተን ስናወጋ በእግረ መንገድ ዘርአይ ደረስ የቅርብ ዘመዷ እንደሆነ አጫወተችኝ። በርግጥ ያለ እውቅናቸው ታሪካቸው ላይ ተረት ከተጨመረባቸው የአፍሪቃ ቀንድ ሰዎች ዘርአይ ደረስ ቀዳሚው ነበር።

ዘርአይ ደረስ በኢትዮጵያ እና በኤርትራ በጀግንነቱ ይታወቃል። በስሙ መንገዶች ተሰይመዋል። በስሙ ትምህርት ቤቶች ተከፍተዋል። በሃይለስላሴና በደርግ ዘመን የዘርአይ ደረስ ታሪክ በአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እንደ መማሪያ ሰነድ ሲያገለግል ቆይቶአል። ወያኔም በዘርአይ ደረስ ስም የሚጠራ ክፍለጦር አቋቁሞአል። ይህ ስመ ገናና ኤርትራዊ ወጣት ኢጣሊያ ላይ ሲገደል ገና የ21 አመት ጎረምሳ ነበር። ከሶፊያ ጋር ስንጨዋወት ዘርአይ ደረስን በተመለከተ እንደምፅፍ ነግሬያት ነበር። ጊዜ ካገኘሁ ወደፊት በተሻለ መልኩ እፅፍበት ይሆናል።

የዘርአይ ደረስ ታሪክ ተጣሞና ተወላግዶ ስለ መፃፉ ከሚጠቁሙ ፅሁፎች መካከል ዘምህረት ዮሃንስ “የኢጣሊያ አገዛዝ በኤርትራ” በሚል ርስስ 2010 ላይ ያሳተመውን መፅሃፍ መጥቀስ ይቻላል። ዘምህረት በመፅሃፉ እንዲህ አስፍሮ ነበር፣

“…የኢትዮጵያ ገዢዎች የኤርትራውያንን ተቃውሞዎች ለኢትዮጵያዊነት ማንነት ሲባል እንደተደረገ ትግል አድርገው ማቅረባቸው ለመስፋፋት አላማቸው መጠቀሚያ ለማድረግ ነበር። የ1937 የሞገስ አስገዶም እና የአብርሃ ደቦጭ ጀግንነታዊ ተግባር፤ እንዲሁም በዚያው አመት ዘርአይ ደረስ በሮማ የፈፀመውን ጀግንነት የኢትዮጵያ ገዢዎች በተከታታይ ለፕሮፓጋንዳ ፍጆታ አውለውታል።

በ1937 ኢጣሊያ የምስራቅ አፍሪቃ ቅኝ ግዛቷን የመሰረተችበትን አንደኛ አመት ክብረ በአል ሮማ ላይ ስታከብር ዘርአይ ደረስ በቦታው ተገኝቶ ነበር። የኢጣሊያ አገዛዝ ትእቢትና ንቀቱን በሚገዛቸው ህዝቦች ላይ በማንፀባረቁ ዘርአይ ደረስ መታገስ ስላልቻለ ተቆጥቶ ጥቂት ኢጣሊያውያንን በጎራዴ ገድሎ፣ ራሱም ቆስሎ ተያዘ። በአንዲት የኢጣሊያ ደሴት እስር ላይ ሳለም አረፈ።

እንደ አንድ የታሪክ ጭብጥ የዘርአይ ደረስ ጉዳይ በቅድሚያ የተፃፈው በኤርትራዊው ብሄረተኛ በወልደአብ ወልደማርያም ነበር። በ1987 ወልደአብ በሰጡት ቃለመጠይቅ ‘በጣሊያን ላይ ያለንን ጥላቻ ለመግለፅ፣ የኤርትራን መንፈስና ጀግንነት ለማጉላት በሚል ነበር በሳምንታዊው ጋዜጣ የዘርአይ ደረስን ጀግንነት የፃፍኩት’ ሲሉ ገልፀው ነበር።

የኢትዮጵያ አገዛዝ ዘርአይ ደረስ የፈፀመውን የጀግንነት ተግባር ለኢትዮጵያዊነት አላማ እንደተፈጸመ በመውሰድ ለፕሮፓጋንዳ ሊጠቀሙበት ሞከሩ…” (“ኢጣሊያዊ መግዛእቲ አብ ኤርትራ” ገፅ 417-418)

የዘምህረት ትንታኔ ኢትዮጵያ ውስጥ ስለ ዘርአይ ደረስ ታሪክ ከሚታወቀው የተለየ ነው። ርግጥ ነው፣ የዘርአይ ደረስ ታሪክ እንደ አቡነ ተክለሃይማኖት እና እንደ ቀዳማዊ ምኒልክ ታሪክ ፈጠራ የታከለበት ተረታዊ ድርሰት መሆኑ እውነት ነው። በኢትዮጵያ ውስጥ በስፋት እንደሚታመነው ዘርአይ ደረስ የሮማ ክብረ በአል ላይ ተቆጥቶ ነጮችን በጎራዴ የለሸለሸው አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ ቀለም ያለው የኢትዮጵያ ባንዴራ ሲረገጥ ተመልክቶ አልነበረም። ገና ከመነሻው በክብረ በአሉ ላይ የኢትዮጵያ ባንዴራ ጨርሶ አልነበረም። በቦታው ያልነበረው ባንዴራ ስለ መረገጡ የተፃፈ ማስረጃም የለም። የባንዴራው የመረገጥ ተረት የሚገኘው በኢትዮጵያ ውስጥ በአንደኛ ደረጃ ትምህርትቤቶች የአማርኛ መልመጃ ላይ ብቻ ነበር። መልመጃውን እያነበበ ያደገ ትውልድ የዘርአይ ደረስን የተጣመመ ታሪክ ወይምበስሙ የተፃፈ ተረት እንደ እውነተኛ ታሪክ አምኖ ቀጠለ። ዛሬ ላይ ቆመን ጊዜውን ስንመዝነው በዘርአይ ደረስ ስሜት ውስጥ ስለ ኢትዮጵያዊነት እና ስለ ኢትዮጵያ ባንዴራ ግንዛቤ ሊኖር የሚችልበት የስነልቦና ሁኔታ አልነበረም። ለኢትዮጵያዊነት ማንነት እና ለኢትዮጵያ ባንዴራ ክብር የታገሉና የተሰው ኤርትራውያን አልነበሩም ማለቴ ግን አይደለም። ነበሩ፣ አሁንምአሉ። ከሞቱት መካከል በጥቂቱ ሎሬንሶ ታእዛዝ፣ ቢትወደድ አስፍሃ፣ ንቡረዕድ ድሜጥሮስና ኮሎኔል ብሽኡን መጥቀስ ሲቻል፤ በህይወት ካሉት ደግሞ ቢያንስ በረከት ስምኦን እና ድምፃዊ አብዱ ኪያር አሉ። የሌሉትን ከመፈለግ ያሉትን ማክበር ቅዱስ ነው።

ርግጥ ነው፣ ዘርአይ ደረስ ለራሱ ለክብሩ ሲል በፈፀመው ጀግንነት እንደ ሰው ልናከብረው ይገባል። ጀግንነቱን እንደ አርአያ ማየትም ቅዱስ ነው። ክፍለጦር ቢሰየምለት፣ የልጆች መማሪያ ቢሆን፣ ባንክ በስሙ፣ መንገድ በስሙ ቢሰየም ይገባዋል። በኢትዮጵያና በኤርትራ ብቻ ሳይሆን ዘርአይ ደረስ በጥቁር ህዝቦች ዘንድ ስሙ ሊዘከር፣ ሊከበር ይገባዋል። የኢትዮጵያን ባንዴራ ግን አያውቀውም ነበርና ከትከሻው ላይ እናውርድለት። በህይወት ለሌሉ ሰዎች ታማኝ መሆን ይጠበቃል።

ከሳባና ከሰለሞን ትረካ ጀምሮ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የተደባለቁትን የፈጠራ ተረቶች ለቅሞ ማውጣት ራሱን የቻለ የሙሉ ጊዜ ስራ ሊሆን ይችላል። እንደ ዘርአይ ደረስ ታሪክ አይነት በህዝብ የታመኑ፤ እንደ ታቦት የሚከበሩ፤ ከተረትነት ወደ ታሪክነት ራሳቸውን ያሳደጉ “ታሪኮችን” መነካካት ዋጋ እንደሚያስከፍልም አውቃለሁ። እንዲህ ያሉ ርእሰ ጉዳዮችን በመነካካቴ ከዚህ ቀደም ብዙ ዋጋ ከፍዬአለሁ። ደግነቱ ቆዳዬ ጠንካራ ነው። በመሆኑም ዛሬም አይነኬዎቹን እየነካሁ ነው። በመሰረቱ ግን አይነኬ የሚባል ታሪክ አለ ብዬ አላምንም። ኢትዮጵያዊነት ነፍስ፣ ስጋና አጥንት ካለው በራሱ አቅም መቆም ይችላል። የፈጠራ ትረካዎች አያስፈልጉትም። ወደ እውነት የተለወጡ የፈጠራ ታሪኮችን መነካካት ወይም መግፈፍ ለኢትዮጵያዊነት ህልውና አስጊ ሊሆን አይችልም።

ርግጥ ነው፣ ተረቶችን ከእውነተኛ ታሪክ የመለየቱ ስራ ቀደም ሲል በአንዳንድ የታሪክ ምሁራን መሞከሩ አልቀረም። ከእነዚህ ሙከራዎች መካከል የተሳካ ስራ የሰራው ታቦር ዋሚ ይመስለኛል። “የውገና ድርሰቶችና የታሪክ እውነቶች” በሚል ርእስ በግእዝ አቆጣጠር 2006 ላይ የታተመውን 660 ገፆች ያሉትን መፅሃፍ ያነበበ ሰው “ታሪክ ፀሃፊ” ደብተሮች ምን ያህል እንደቀለዱብን በቀላሉ መገንዘብ ይችላል።

*Gadaa Ghebreab can be reached at : ttgebreab@gmail.com

Leave a comment